Welcome!

"If you are neutral 0n the situations of injustice, You have choosen the side of oppressors." -Desmond tutu

Friday, May 3, 2013

ሦስት:- ደፋርና ጭስ መውጫ አያጣም! የኢትዮጵያ ሳታላይት ቴሌቪዢንና ራድዮ



እስካሁን ድረስ ያሳየነው ችሎታ የማጥፋት ወይም የማክሸፍ እንጂ አዲስ ነገርን ወይም አዲስ ሥርዓትን የመፍጠር አይደለም፤ በአለፉት ሃምሳ ዓመታት ውስጥ ቢያንስ ሦስት የአስተዳደር ሀሳቦች መቅረባቸውን አውቃለሁ፤ አንዱ በአቶ ሀዲስ አለማየሁ፤ ሁለተኛው በኤንጂኒር-የሕግ ባለሙያ ደመቀ መታፈሪያ፣ ሦስተኛው የኔ ናቸው

አእምሮአቸውና ልባቸው በማርክሳዊ-ሌኒናዊ ጦር ተቀስፎ የተያዘባቸው ወጣቶች ሌላ ሀሳብን የማይሰሙበት ጊዜ ነበር፤ ማርክሳዊ-ሌኒናዊ ጥራዝ-ነጠቅነት ብቻ የሁሉም ዓይነት የእውቀት ምንጭ ብለው በጭፍን የሚያምኑ ወጣቶች በተለይም ከኢትዮጵያዊ የፈለቀ ሀሳብን ለማጥላላት ጉልበታቸውንና ጊዜያቸውን አይቆጥቡም ነበር፤ የሌኒን የጡት ልጆች እርስበርሳቸው ተፋጁና ያሸነፉት ዛሬም ከፋፍለው ይገዙናል፤ የት እንደሚያደርሱን ገና አላወቅንም።

ለኢትዮጵያ ለዘለቄታው ይበጃል የምንለውን የፖሊቲካ እምነትና ሥርዓት እኛው ራሳችን አምጠን ብንወልደው መልካም መሆኑ አይጠረጠርም፤ ግን ከላይ እንደገለጽሁት የኛ ችሎታ ማጨናገፍ ነው እንጂ ወላድና አዋላጅ መሆን አይደለም፤ እሰከዛሬ ለሁሉም የሚሆን መድረክ አልነበረምና መተባበሩ ችግር ሊሆን ይችል ነበር ይሆናል፤ አሁን ግን ኢሳት ሁሉንም ዓይነትና እምነት በእኩልነት ያስተናግዳል፤ ወይም ለማስተናገድ የሚችል ይመስለኛል፤ አሁን በኢሳት የሚሰማው የከሸፈ ቀረርቶና የተስፋ ቀረርቶ ነው
 
የከሸፋን ቀረርቶ እንደታሪክ ትምህርት እንዳንወስደው ጠያቂና ተጠያቂ ሆነው የሚቀርቡት ተጠያቂው አዋቂ ጠያቂው የማያውቅ ሆነው ነው፤ ለዚህም ነው የከሸፈ ቀረርቶ የሚሆነው፤ የተስፋው ቀረርቶም እንዲሁ ነው፤ በኢሳት መድረክ ላይ የሚናገሩት ሰዎች ከአወያዩ ወይም ከጠያቂው ሌላ ሁለት ወይም ሦስት ቢሆኑ አንዱ ሌላውን እያፋጠጠ እውነቱ ሊነጥርና ሀሳብ ሊበጠር ይችል ነበር፤ በውይይት ወይም በክርክር ስላለፈው ለመማር ስለወደፊቱ ለማቀድ ምቹ ይሆን ነበር፤ ለየብቻ ሜዳ እየሰጡ የፉከራ ወይም የማቅራሪያ መድረክ ማድረጉ ግን ብዙ አያራምድም፤ ሁሉም እንደታማኝ ተጨባጭ የምስል ማስረጃዎቹን ይዞ መቅረብ የሚችል ቢሆን እንኳን አንዱን የቀረርቶ ዓይነት ያስቀረዋል ለማለት ይቻላል፤ በተረፈ ግን በቀረርቶ አንማርም፤ በቀረርቶ አናቅድም።

መድረኩን ለየብቻቸው የሚፈልጉት ሰዎች ያለጥርጥር በውስጣቸው አምባ-ገነንት ለመኖሩ ምልክት እያሳዩ ነው፤ የሚሞግታቸው ወይም በጥያቄ የሚወጥራቸው ሰውን የማይፈልጉ ከሆነ ለምን ይጠቅሙናል? እንደዚህ ያሉ ሰዎችንስ መቼ አጣን? በቴሌቪዥኑ ጸዳል ለመሞቅ ብቻ የሚፈልገውን ማስተናገድ ለሌላው አይጠቅምም፤ ከባህላችን የወረስነውን ድካም እያስተነገድን ነው፤ ይህ ለአጠቃላይ ለውጥ እንደማይበጅ የተረጋገጠ ይመስለኛል፤ ይህ ካልተረጋገጠ የኢሳት ልፋት ለምንድን ነው

በኢሳት ላይ የሚቀርበው ሁሉ ስለዴሞክራሲ ይሰብካል፤ ነገር ግን በተግባር ዴሞክራሲ የሚገለጥበትን መንገድ ውይይትና ክርክር አያሳዩም፤ ለምሳሌ ሁለቱ ኦነጎች፣ ሁለቱ ኢሕአፓዎች፣ የጎሣ ድርጅትን እንደፖሊቲካ ፓርቲ የሚቀበሉና የማይቀበሉ፤ ለኢትዮጵያ የሚበጀው ምን ዓይነት የኢኮኖሚ ሥርዓት እንደሆነ የተለያየ አቅዋም ያላቸው ሁሉ ፊት-ለፊት እየገጠሙ ሲከራከሩ አናይም፤ መድረኩን ለየብቻ ካልያዙት በቀር አንደበታቸው አይፈታም፤ በአጭሩ እየተሰበከ ያለው ዴሞክራሲ በኢሳት መድረክ ላይ አይታይም፤ መቼ ሊጀምር ታስቦ ነው?

እኛው ራሳችን በፈጠርነው መሠረት ላይ አብዛኞቻችንን ኢትዮጵያውያን የማይጎረብጥ ሥርዓት ለመገንባት ፍላጎት ያደረብን ይመስላል፤ ኢሳት ከአንድ ባህላዊ ችግር ሰብሮ የወጣ አስተሳሰብ ላይ የቆመ ነው ለማለትም ሳይቻል አይቀርም፤ የጉልበተኛነትን ባህል በነገረኛነት ባህል እንተካው የሚል ይመስላል፤ ከላይ ስጀምር ኢሳት የባህል ይዘት አለበት ያልሁት ነገረኛነትን ነው፤ ኢሳት የጠምንጃ-ያዥነትንና የጉልበተኛነትን ትምክህት ‹‹አከርካሪውን ሰብሮ›› የነገረኛነትን ባህል ስር ለማጠናከር የሚጥር ይመስላል፤ ይመስላል ከምል ነው ብል ደስ ይለኝ ነበር፤ ነገር ግን ብዙ ወሬዎች ይሰማሉ።

ኢሳት አንድ ልዩ ተልእኮ ያለው ቡድን የሚጋልበው ፈረስ ነው ይባላል፤ ኢሳት እንደተለመደው የጥቂት ሰዎችን ኑሮ ለማመቻቸት ገንዘብ መሰብሰቢያ ነው ይባላል፤ ጨረቃንና ጸሐይን ምሥጢር ማድረግ ባህላችን ነው፤ ለማናቸውም ዓይነት ሙከራ የተለየ ዓላማ መስጠት ባህላችን ነው፤ ኢሳትን የፈጠረውን ዓይነት ጉልህ የመተባበር ውጤት ለማስተጓጎል ባህላዊ መሰናክሎች እንደሚፈጠሩ ሳይታለም የተፈታ ነው፤ እነዚህን መሰናክሎች ማስወገድ የምንችለው ሌሎች የዴሞክራሲ ባሕርዮችን፣ ማለትም ግልጽነትንና ተጠያቂነትን የአሠራር ልምድ በማድረግ ብቻ ነው፤ የማሞኘትና የብልጣብልጥ መንገዶች ሁሉ ተሞክረው ወደገደል አፋፍ የሚያመሩ ኮረኮንች መሆናቸውን ሁሉም አውቆታል፤ ጥርጣሬዎች የሚነሡትም በሁለት ምክንያቶች ነው፤ አንዱ ግልጽነትና ተአማኒነት ሲጎድል ነው፤ ሁለተኛው ቀደም ሲል በተለያዩ ቡድኖች የተተለሙትንና የከሸፉትን ሙከራዎች በማስታወስ ነው፤ በዚያ ላይ ጥርጣሬን የሚሰብከው ባህላችን አለ።

የኢሳት ልዩ ዓላማ ምንም ይሁን ምን የኢትዮጵያንና የኢትዮጵያን ሕዝብ አጠቃላይ ዓላማ የሚያራምድ ከሆነና ለማናቸውም ኢትዮጵያዊ አመለካከት በሩን ክፍት አድርጎ ካስተናገደ ከዚህ በላይ የሚጠበቅበት ተግባር ያለ አይመስለኝም፤ ማናቸውም ዓይነት ሀሳብ፣ ማናቸውም ዓይነት አመለካከት፣ ማናቸውም ዓይነት የፖሊቲካ እምነት በነጻነት የሚነገርበት መድረክ ከሆነ፣ ማናቸውም ዓይነት ሀሳብ፣ አመለካከትና የፖሊቲካ እምነት ያላቸው ሰዎች በግልጽና በነጻነት የሚወያዩበት ወይም የሚከራከሩበት መድረክ ከሆነ ሌላ ምን ይፈለጋል? ወያኔ/ኢሕአዴግ የዘጋው ይህንን ነው፤ ኢሳት ይህንን በር ለሁሉም ከከፈተ ኢትዮጵያውያን ከመታፈን ዳኑ ማለት ነው፤ ስለዚህም የባለቤትነቱ ጉዳይ ችግር ሊፈጥርብን አያስፈልግም።

የኢሳት ዋና ጥቅሙ የኢትዮጵያን ሕዝብ ከወያኔ/ኢሕአዴግ አፈና ለማዳን ብቻ አይደለም፤ ከዚያ በጣም የበለጠና ለዘለቄታው ጠቃሚ የሆነ ነገር አለ፤ ይህም ለኢትዮጵያ ሕዝብ የዴሞክራሲን ባህል ማስተማር ነው፤ እኔ የዴሞክራሲ ባህል የምለው በነጻነት ላይ ቆሞ ነጻነትን እያራገበ በልበ-ሙሉነት የሌሎችን ነጻነት የሚያከብርና የሚያስከብር ቃልና ተግባር የተስማሙበትና በሕግ ልዕልና የሚዳኙበት ሁኔታ ውስጥ መሆንን ነው፤ ይህንን ባህል በኢትዮጵያ ሕዝብ ኅሊና ውስጥ ለመትከል ቀላል አይደለም፤ በመጀመሪያ በኢሳት ውስጥ የሚሠሩት ሰዎች ለዚህ ጥሩ አርአያ ሆነው መታየት አለባቸው (ጓደኛቸው የተለየ ሀሳብ ሲያቀርብ ግር የሚላቸው በኢሳት ውስጥ እንዳሉ ከአንዴም ሁለቴ ታዝቤአለሁ፤)
 
የተለየ ሀሳብን ለመስማት የማንፈራ ለመሆን መማር ያስፈልገናል፤ አቶ መለስ ዜናዊ የተለየ ሀሳብን የመስማት ችሎታ ቢያዳብር በአበበ ገላው ውርጅብኝ አንገቱን ለዘለዓለም አይደፋም ነበር፤ መቻቻልና መከባበር በዴሞክራሲ የሚመጣ ልዩ ችሎታ ነው፤ ይህ ችሎታ እንደሌለን አውቀንና አምነን ከተነሣን ኢሳት ድንቅ መሣሪያ ይሆንልናል፤ እኛም ኢሳት እንዲከበርና ድምጹ ዋጋ ያለው እንዲሆን ለማድረግ እንችላለን፤ ኢሳት የኢትዮጵያን ሕዝብ በዴሞክራሲ ሲያበለጽግና ሲያጎለብት፣ የኢትዮጵያ ሕዝብም ኢሳትን ማበልጸግና ማጎልበት የሚጠበቅበት ይመስለኛል።

No comments:

Post a Comment